
“ቢቻላቹስ በእናንተ በኩል ከሰው ሁሉ ጋር በሰላም ኑሩ፡፡ ሮሜ 12÷18
ከእግዚአብሔር ለመስማት ከፈለግን ለመገኘቱ የሚመች ሁኔታዎችን መፍጠር አለብን፡፡ ሁኔታ ሲባል ምቹ የሆነ አካባቢ ማመቻቸት ማለት ነው፡፡ አካባቢ በሁኔታዎች የሚፈጠር ግንኙነትን ሊያሳምር ወይም ሊያደናቅፍ የሚችል ነው፡፡ ከእግዚአብሔር ለመስማት ሠላማዊ አካባቢ ያስፈልጋል፡፡ እኛም መልሰን ሠላምን የምናገኘው በራሳችን ሁኔታ የእግዚአብሔርን ሠላም በእምነትና በፈቃዳችን ለሌሎች ይቅርታ ስናደርግ የምናገኘው ነው፡፡
ጥል ወይም ሁከት ባለበት ቦታ አካባቢው ወይም ሁኔታው ሠላም ሳይን ሁከት ነው የሚቆጣጠረው፡፡ ልክ እንደዛው የሠላም ስሜት የሚሰማው ሰዎችና ሁኔታዎች በሠላም ድባብ ውስጥ ሲገኙ ነው፡፡ ስለዚህ እኛ መሥራት ያለብን በሄድንበት ቦታ ሁሉ ሠላምና የሠላም ድባብ እንዲፈጠር ነው፡፡ ምክንያቱም ከእግዚአብሔር ድምፅ ለመስማት በሁከት ውስጥ ስለሚያዳግት ነው፡፡ ሁከትና መለያየት ባለበት ሁኔታ ውስጥ እግዚአብሔር አይናገርም፡፡ ነገር ግን እግዚአብሔር በሰላማዊ ሁኔታ ውስጥ የሰው ልብና አእምሮ በሠላም በፍቅር ሲሞላ ነው፡፡
በእግዚአብሔር መገኘት ሙላት ለመደሰት ከፈለግን በአካባቢያችን ያለውን ሁኔታና በልባችን እራሱን ማክበር አለብን፡፡ ከእግዚአብሔር ለመስማት ከፈለግን ለእርሱ የማይመቹ ክፉ ባሕሪያችንን ለጌታችን ክርስቶስ በማስረከብ ምቹ ሁኔታን በመፍጠር መገኘቱንና የእርሱን ድምፅ መስማት እንችላለን፡፡
ዛሬ የእግዚአብሔር ድምፅ ለአንተ፡- ተግባርህን ሠላም ፈጣሪ አድርግ፡፡