የመጽናት ኃይል

በዚያን ጊዜ ሰውየው፣ “እንግዲህ መንጋቱ ስለ ሆነ ልቀቀኝና ልሂድ” አለው። ያዕቆብም፣ “ካልባረክኸኝ አልለቅህም” አለው። (ዘፍጥረት 32፡26)

አንዳንድ ጊዜ ጥቂት ቃላትን ወይም ጥቂት ዓረፍተ ነገሮችን በአንድ ጊዜ ትጸልይና ከዚያ በኋላ በፍጹም ስለዚያ ነገር አታስብም። በሌላ ጊዜ ግን፣ አንድ ሰው ወይም ሁኔታ ወደ ልብህ ተመልሶ መምጣቱን ይቀጥላል እናም ስለዚያ ነገር መጸለይ እንዳልጨረስክ ታውቃለህ። መንፈስ ቅዱስ አንድን ነገር ደጋግሞ ሲያሳስብህ፣ ምናልባት ያለማቋረጥ በጽናት መጸለይ እንድትቀጥል፣ ተስፋ ለመቁረጥ ፈቃደኛ ላለመሆን ጸሎቶችን እንድትጸልይ ሳይሆን አይቀርም።

በሕይወቴ የእግዚአብሔር ፈቃድ መሆናቸውን የማውቃቸው ነገሮች አሉ፤ምክንያቱም በግልጽ በቃሉ ውስጥ ስለእነርሱ ተናግሯል። ስለእነሱ ስጸልይ እና ለውጥ ከሌለኝ ተመልሼ ወደ እግዚአብሔር እሄድና “እንደገና መጥቻለሁ። እናም እግዚአብሔር ሆይ፣ አንተን አለማክበር አይደለም፣ ነገር ግን ለውጥ እስከማገኝ ድረስ ዝም አልልም።” አንዳንድ ጊዜ “ጌታ ሆይ እንደገና እየጠየቅኩህ ነው፣ደግሞም በዚህ ዙሪያ ድልን እስካይ ድረስ መጠየቄን እቀጥላለሁ።” እላለሁ። በሌሎች ጊዜያት ደግሞ እየሰራ ስላለው ነገር እግዚአብሔርን እያመሰገንኩት ድልን እንደምጠብቅ ደግሞ አስታውሰዋለሁ። እኛ እንደ ያዕቆብ ሆነን “እስክትባርከኝ ድረስ አልለቅህም” ማለት አለብን። እግዚአብሔር ያዕቆብን በእርግጥ ባርኮት ነበር፤ ምክንያቱም ያዕቆብ በሰው እና በእግዚአብሔር ዘንድ እንዴት አሸናፊ መሆን እንደሚችል የሚያውቅ ሰው ነበር። በሌላ አገላለጽ ያዕቆብ ጽኑ ነበር እናም ተስፋ አልቆረጠም (ዘፍጥረት 32:24–28 ን ተመልከት)!

የእግዚአብሔርን ፈቃድ ሳውቅ፣ በዚያ መሠረት መጸለይ እችላለሁ ደግሞም ተስፋ ለመቁረጥ እምቢ ማለት እችላለሁ።እግዚአብሔር በቆራጥ ሰው ደስ ይለዋል እናም እንዳንደክም ወይም እንዳንዝል በቃሉ ያበረታታናል። መጽናት ዋጋ ያስገኛል፣ ስለሆነም ፀሎትህን ጨምሮ በሁሉም የሕይወት ግቦችህ ላይ ቆይ። ከቁርጠኝነት የተነሳ ያዕቆብ በእግዚአብሔር እና በሰው ዘንድ አሸነፈ ደግሞም በአዲስ ስም እና በህይወት አዲስ ጅማሬን ተሸልሟል።


ዛሬ የእግዚአብሔር ቃል ለአንተ፡ እግዚአብሔር በአክብሮት መጽናት ደስ ያሰኘዋል።

Facebook icon Twitter icon Instagram icon Pinterest icon Google+ icon YouTube icon LinkedIn icon Contact icon