ብትወዱኝ ትእዛዜን ጠብቁ (ታዘዙ) ። (ዮሐንስ 14 15)
በዛሬው ክፍል፣ ኢየሱስ ለእርሱ ያለንን ፍቅር እርሱን በመታዘዝ እንደምናሳይ ይናገራል። ከእግዚአብሔር ስለ መስማት ባሰብኩ ቁጥር ሁሉ፣ ቀደም ሲል ማድረግ እንዳለብን በምናውቀው ነገር ካልታዘዝነው እሱን በግልፅ መስማት አንችልም ወደ ሚለው እውነት እመለሳለሁ። ባለመታዘዝ የሚወቅስ ህሊና ይኖረናል። ያ የሚወቅስ ሕሊና እስካለን ድረስ እምነት እና ድፍረት ሊኖረን አይችልም (1 ዮሐንስ 3፡20-24 ን ተመልከት) ።
የክርስቲያን ግቦች ከማያምን ሰው ግቦች በጣም የተለዩ መሆን አለባቸው። እግዚአብሔርን የማያገለግሉ ሰዎች ገንዘብን፣ ቦታን፣ ሀይልን እና ነገሮችን ይፈልጋሉ፣ ነገር ግን እንደ ክርስቲያኖች ዋናው ግባችን እግዚአብሔርን መታዘዝ እና ማክበር መሆን አለበት። እግዚአብሔርን ስለመታዘዝ ብዙም ሳላስብ ለብዙ ዓመታት ወደ ቤተክርስቲያን ሄጃለሁ። በእግዚአብሔር ዘንድ ተቀባይነት እንዳገኝ ያደርገኛል ብዬ ተስፋ በማድረግ ሃይማኖታዊ ቀመር እከተል ነበር፣ ነገር ግን በየቀኑ በእርሱ መርሆዎች ለመመራት ሙሉ ቃል አልገባሁም። መላ ሕይወትህን ለእግዚአብሔር ክፈት እና መንፈስ ቅዱስን የህይወትህ አስተማሪ አድርገህ ወደህይወትህ ጋብዝ። የእርሱን መመሪያዎች ለመታዘዝ የተቻለህን ሁሉ አድርግ፣ ስትሳሳት ምህረትን ጠይቅ እና እንደገና ጀምር። የጥፋተኝነት ስሜትህን እያዳመጥክ ጊዜ እና ጉልበት አታባክን፣ ምክንያቱም በክርስቶስ ሁል ጊዜ አዲስ ጅማሬ ማግኘት እንችላለን። ስለ መታዘዝ ጸልይ፣ አጥና ደግሞም በየቀኑ በንቃት ተከታተል። በዚህ መንገድ ለእግዚአብሔር ያለንን ፍቅር እናሳያለን።
ዛሬ የእግዚአብሔር ቃል ለአንተ፡ የቱንም ያህል ላለመሳሳት ብንጥርም ሁላችንም እንሳሳታለን፣ ነገር ግን ለመተው ፈቃደኛ እስካልሆንን ድረስ ግቦቻችን ላይ እንደርሳለን።