በዚህም እጅግ ደስ ይላችኋል፥ ነገር ግን በእሳት ምንም ቢፈተን ከሚጠፋው ወርቅ ይልቅ አብልጦ የሚከብር የተፈተነ እምነታችሁ፥ ኢየሱስ ክርስቶስ ሲገለጥ፥ ለምስጋናና ለክብር ለውዳሴም ይገኝ ዘንድ አሁን ለጥቂት ጊዜ ቢያስፈልግ በልዩ ልዩ ፈተና አዝናችኋል። – 1 ጴጥ 1፡6-7
ስብራት የሚለው ቃል በአንዳንድ ሰዎች ልብ ውስጥ ፍርሃትን ሊፈጥር ይችል ይሆናል፡፡ ሆኖም ግን ቃሉ መጥፎ ትርጉም ያለው ቃል አይደለም፡፡ እግዚአብሔር መንፈሳችንን የመስበር ፍላጎት የለውም፡፡ሆኖም ግን በእኛ ውስጥ እና መሆንና ማድረግ የሚፈልገውን ነገር እንዳያደርግ የሚከለክሉትን ነገሮች መስበር ይፈልጋል፡፡ በእኛ ውስጥ ያሉትን ትምክህትን፣ አመጽን፣ ራስ ወዳድነትን፣ ግለኝነትን መስበር ይፈልጋል፡፡ እግዚአብሔር ሙሉ ለሙሉ በእርሱ ላይ እንድንደገፍ ይፈልጋል ፣ መከራ ደግሞ ወደዚህ ደረጃ እንድንመጣ የሚያደርገን ይመስላል፡፡
አንዳንድ ጊዜ ሰዎች በመከራና በፈተናዎች ውስጥ ማለፍ አለባችሁ ሲባሉ ሲገረሙ ይታያል፡፡ እንደውም የእግዚአብሔርን ቃል ለመማርና ለመታዘዝ ታማኞች ሆነን ሳለን እንኳ ፈተናዎች ወደ እኛ ይመጣሉ። አንዳንድ ጊዜ ፈተናዎችና መከራዎች የሚመጡት እምነታችንን ለመፈተንና ለማጥራት ነው፡፡
እነዚህ ፈተናዎች በመንገዳችሁ ላይ በሚመጡበት ጊዜ ተቀበሏቸው ምክንያቱም ወደ እውነተኛ ስብራት ይመሯችኋልና፡፡ እግዚአብሔር በስጋ ሳይሆን በመንፈስ እንድንኖር ይፈልጋል፡፡ ይሄ ቀላል የሚሆነው ግን እግዚብሔር በውስጣችን ያለውን ኃጢያተኛ ማንነትና ሕይወታችንን ከእርሱ የሚከለክለውን ማንኛውንም ባህሪያቶች እንዲሰብርልን ስንፈቅድለት ነው፡፡ ዛሬ ወደ እግዚአብሔር መቅረብ ትፈልጋላችሁ? እንግዲያውስ የነገ ሕይወታችሁን ወደ ታላቅነት እንደሚመራ በማወቅ የውስጥ ስብራትን እንቀበል፡፡
ጸሎት ማስጀመሪያ
መንፈስ ቅዱስ ሆይ ፣ አንዳንድ ጊዜ ውስጣዊ ስብራት እንደሚያስፈልገኝ ተገንዝቤያለሁ፡፡ የሚመች ላይሆን ይችላል ነገር ግን ከአንተ የሚለየኝን ማንኛውንም ነገር ከውስጤ ሰብረህ እንድታስወግደው እጋብዝሃለሁ፡፡